25/07/2022
+ አበረታች መድኃኒት +
የአበረታች መድኃኒት ጉዳይ የአትሌቲክሱን ዓለም ሲያምሰው የሚኖር ጉዳይ ነው፡፡ በስፖርታዊ ጨዋታዎች ላይ የአሸናፊነት ሜዳሊያ አጥልቀው ፈንጠዘው የሀገራቸውን ሰው ያስፈነጠዙ አትሌቶች ‹ጉድና ጅራታቸው› ከወደኋላ መጥቶ ያስመዘገቡትን ድል እየተቀሙ ፣ ሐፍረት ሲከናነቡ ይታያል፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ማሸነፍ የቻሉት በድካማቸው ብቻ ሳይሆን ‹በሚወስዱት መድኃኒት› ሆኖ በመገኘቱና ኃይል ሰጪ መድኃኒት ወስደው ከሰው ጋር የማይመጣጠን ጉልበት ጨምረው በመግባታቸው ነው፡፡
ይህንን ዜና ስንሰማ ብዙዎቻችን አንዲት ኢትዮጵያዊት ጀግና አትሌት ትዝ ሳትለን አልቀረችም፡፡ ይህች አትሌት የለንደን ኦሎምፒክ የ5000 ሜትር የሴቶች የወርቅ ሜዳልያ አሸናፊዋ ጀግናዋ አትሌት መሠረት ደፋር ናት፡፡ መሠረት ደፋር አበረታች መድኃኒት በመውሰድ ብቻ ሳይሆን አበረታች መድኃኒቷን እዚያው የመሮጫ ትራኩ ላይ አውጥታ ያሳየችና ወደ ካሜራ ቀረብ አድርጋ ለዓለም ‹አበረታች መድኃኒቴ ይኼ ነው!› ብላ ያሳየች ጀግና ናት - እውነትም መሠረት ደፋር!
ከራሴ ልጀምር፡፡ የ2012ቱ የለንደን ኦሎምፒክ በተካሔደበት ወቅት የነበርሁት ከፍተኛ ሙቀት ካለበት በመካከለኛው ምሥራቅ በተባበሩት የአረብ ኢመሬትስ የአቡዳቢ ከተማ ነበር፡፡ ሙቀቱም ማቀዝቀዣውም የሚመች ባለመሆኑ የአየሩ ሁኔታ አድካሚና ተኝተው ሲነቁ ዳግመኛ መተኛት የሚያሰኝ ዓይነት ነበር፡፡ በሌሊት የሚተላለፈውን የነመሠረትን የሩጫ ውድድር እንድመለከት አብረውኝ የነበሩት ሰዎች ሲቀሰቅሱኝም ከአልጋ የተነሣሁት በብስጭትና በይሉኝታ ሩጫው ከተጋመሰ በኋላ ነበር፡፡ የሩጫው የመጨረሻ ሰዓት ላይ መሠረት አስደናቂውን ድል አስመዘገበች፡፡ እንደ ሁሉም ኢትዮጵያዊ እኛም በደስታ አጨበጨብን፡፡
ከዚህ በኋላ መሠረት ባንዲራ ለብሳ ስትሮጥ ለማየት ስንጠባበቅ አንዳች ነገር ከደረቷ አውጥታ ተንበረከከች፡፡ ከደረቷ ባወጣችው ጨርቅ መሰል ነገር ፊቷን ሸፍና አቀርቅራ ታለቅስ ጀመር፡፡ ቀና ስትል ግን በፊቷ ላይ የለጠፈችው ድንግል ማርያምን ከተወደደ ልጇ ጋር የሚያሳይ ሥዕል ነበር፡፡ የሁላችንም ዕንባ ሳናስበው ከዓይናችን ወረደ፡፡
መሠረት ሥዕሉን ከፊቷ ላይ አንሥታ ከተንበረከከችበት ተነሣች፡፡ የእመቤታችንን ሥዕልም ወደላይ ከፍ አድርጋ አሳየች ፤ ወደ ካሜራውም አቀረበችው ፤ ኦሎምፒክን ለሚመለከተው የዓለም ሕዝብ መሠረት ሥዕለ ማርያምን አሳለመችው፡፡ እመቤታችንን የሚወዱ በትኩስ ዕንባ ፤ እርስዋን የሚጠሉ ደግሞ በንዴት ተቃጠሉ፡፡ መሠረት ያቀፈቻትን ድንግል ማየት ባይወዱ እንኳን ድንግል ያቀፈችውን ጌታ ማየት ቢችሉ ምን ነበረበት?
ይህን ካየሁ በኋላ እኔም እንቅልፌ ጠፋ ፤ ከየአቅጣጫው ስለ መሠረት የሚባለውን ስፈላልግ ነጋ፡፡
ጨዋታውን የሚያስተላልፉት ኮሜንታተሮች ምን እንደሚሉ ግራ ተጋቡ፡፡ ልክ የእመቤታችንን ሥዕል ሲታይ እንዲህ ተባብለው ነበር ፡-
ኮሜንታተር 1 - ተመልከት ... አአአህ! (ሥዕሉ ቀርቦ ሲታይ) ያው እንደሚታወቀው በአንዳንድ ቦታዎች ይኼ ነገር መልእክት ይኖረዋል ፤ አይደል እንዴ?
ኮሜንታተር 2 - አዎ በኢትዮጵያ ጠንካራ የክርስቲያን ማኅበረሰብ አለ ...
ኮሜንታተር 1 - አዎ .. አዎ ... እናም እንደሚመስለኝ እእ... የምንመለከተው ነገር ...... እእእ.... አሥራ አምስት ፣ ዜሮ አራት ከሃያ አምስት ... መሠረት ደፋር!! ብሎ አቆመ፡፡ መሠረት እኛን ብቻ ሳይሆን ኮሜንታተሩንም የሚናገረውን አሳጣችው፡፡ የሩጫውን አደባባይ ዐውደ ምሕረት አድርጋበት የማያውቀውን ጉባኤ መምራት ከየት ያምጣው?
ወዲያውኑ የዜና አውታሮችና በዓለም ዙሪያ ያሉ ድንግል ማርያምን የሚወዱ ክርስቲያኖች ስለመሠረት ደፋር የተሰማቸውን ለመግለጽ ተሽቀዳደሙ፡፡
አሶሺየትድ ፕሬስ መሠረት ያሳያችውን ሥዕለ ማርያም ‹ፎቶ› ብሎ ብቻ ሊያድበሰብሰው ሲሞክር ሮይተርስ ግን ‹ሃይማኖታዊ ሥዕል ያለበት ከጨርቅ የተሠራ..› ብሎ ገልጾታል፡፡ የዜናው አዘጋገብ ያልተመቻቸው ብዙ ክርስቲያኖች በተለይ አሶሺየትድ ፕሬስ ላይ ትችታቸውን አዝንመዋል፡፡ በአንጻሩ ሃይማኖታዊ ሚድያዎች ደስታቸውን የሚገልጽ ዘገባ ይዘው ቀረቡ፡፡ የካቶሊክ ዜና አገልግሎት (CNA) ‹ድንግል ማርያም ከኦሎምፒክ ወርቅ አሸናፊዋ ጋር የመጨረሻውን መስመር አብራ ተሻገረች!› ሲል ዘገባውን አወጣ፡፡ ኤክዛማይነር ዶት ኮም የተሰኘው ድረ ገጽ ደግሞ ‹‹ድንግል ማርያምና ሕጻኑ ክርስቶስ በኦሎምፒክ አምስት ሺህ ሜትር ውድድር ላይ (ታዩ)!›› ብሎ አወጣ፡፡ በማኅበራዊ ሚድያም ብዙዎች ደስታቸውን ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያውያን ፣ ግብፃውያን ፣ ላቲን አሜሪካዊያን ፣ ስፔናዊያን ሌሎችም በማኅበራዊ ሚድያ የመሠረትን ምስክርነት እንዲህ አደነቁ፡፡
‹ዕንባዬን ማቆም አልቻልኩም!›
‹ኢትዮጵያውያን የተባረኩ ናቸው ፤ ቅዱሱ ጽዋ እነርሱ ጋር እንደሆነ አንብቤያለሁ!›
‹መሠረት ደፋር እንኳን ደስ አለሽ ፤ ክርስትናችንን ስለመሰከርሽልን እናመሰግናለን!›
‹ማታ ስመለከተው ከዓይኔ ዕንባ ፈለቀ ፤ ያየሁት NBC ላይ ነበር ፤ ካሜራው ግን ለምን ቶሎ ወደ ሌላ ቦታ አዞረው?›
‹ኮሜንታተሮቹን አልወደድኳቸውም ፣ ምን ያህል ስሜት የሚነካ ቅጽበት እንደነበር አልገባቸውም›
‹የዐሥራ አምስት ዓመት ልጄ አገር አቋራጭ (XC) እና የትራክ ውድድር ትሮጣለች፡፡መሠረትን ስታይ ‹ኦ! ከዚህ በኋላ የቅድስት እናታችንን ሥዕል ይዤ መሮጥ መጀመር አለብኝ› አለች!›
የመሠረት ምስክርነት በማኅበራዊ ሚድያ ብቻ ሳይወሰን ወደ ቤተ መቅደስም ገብቶ የስብከት ርዕስ ሆነ፡፡ እርስዋ አርብ ለቅዳሜ አሸንፋ ያሳየችውን ነገር እሑድ የሰንበት ቅዳሴ ከተቀደሰ በኋላ አቡነ ቄርሎስ ጊዮርጊስ የተባሉ ግብጻዊ አባት በሎስ አንጀለስ በሚገኘው የቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን አስተማሩበት፡፡
‹‹ከእናንተ መካከል ትናንት የኦሎምፒክ ጨዋታ ያየ ማን ነው? በአምስት ሺህ ሜትር ሴቶች ያሸነፈችውን ኢትዮጵያዊት ወጣት አላያችኋትም? መጀመሪያ ሦስተኛ ደረጃ ላይ ሆና ነበር የሮጠችው፡፡ ውድድሩ ሊያልቅ ጥቂት ሰከንዶች ሲቀሩት ግን አንደኛ ሆነች፡፡ ሩጫውን ስትጨርስ ተንበረከከች... በነገራችን ላይ የምነግራችሁ ዓለም ሁሉ ስለሚመለከተው ኦሎምፒክ ነው ... ከደረትዋ የሆነ ነገር ለማውጣት ታገለች ... አወጣችው ... ምን እንዳወጣች ታውቃላችሁ? ... የድንግል ማርያምን ሥዕል! ... ኢትዮጵያዊት ስለሆነች ያወጣችው ሥዕል በእኛ ቤተ ክርስቲያን እንዳለው ዓይነት ሥዕለ ማርያም ነበር .. ወደ ካሜራው አስጠጋችው .. በጣም ደስ ብሏታል ... አምስት ሺህ ሜትር አሸንፋ ነው እንግዲህ ... ስሟም ደፋር ይባላል ... ስታሸንፍ ግን ቅድስት ማርያምን አሳየች ... አያችሁ ድንግል ማርያም እኮ ትወደዳለች!›
አዎ በዚያች ምሽት መሠረት የብዙኃንን ልብ በደስታ ሞልታው ነበር፡፡ የባሕርያችንን መመኪያ ወላዲተ አምላክን በዓለም አደባባይ ስታሳየን ልባችን በደስታ ተሞላ .. አንድ ወዳጄ ይህን ነገረኝ ‹‹ሆስፒታል ስለምሠራ የዚያን ዕለት አዳሪ ነበርሁ ... የሆስፒታሉ ሠራተኞች እና ሕሙማን ውድድሩን ይመለከቱ ነበር ... መሠረት ስታሸንፍ ሁሉም በአንድነት ጮኸ ተደሰተ ... ጥቂት ቆይቶ የእመቤታችንን ሥዕል ሲታይ ግን የታመሙት ሳይቀሩ ከአልጋቸው እየተነሡ ፈነደቁ ... መሬት ሳሙ...››
በዚያች ምሽት የእመቤታችን ወዳጅ ሆኖ መሠረትን ‹ዕድሜ ይስጥሽ ፣ እመብርሃን ትባርክሽ!› ያላላት ሰው አልነበረም፡፡ በዚያች ምሽት የማይዘነጋ ፣ ከልብ የማይወጣ ትልቅ ስብከት ተሰበከ!
መ/ር አቡኑ ማሞ የተባሉ ካህን በዚያች ዕለት በገጠሙት ግጥማቸው እንዳሉት በእርግጥም ‹ለንደን ግሸን ሆነች!›... እርሳቸው ልብ የሚነካ ግጥማቸው ይህን ጽሑፍ ያሳርጉልናል :-
የእሳት ትንታግ ፍንጣሪ
የድል ዜማ ወገን አኩሪ
የክብር ጥግ ማማ
የደስታ ውበት ቄጤማ
የመስቀሉን ኃይል ከግሸን የጠበሉን በረከት ዘግና
ይኸው አየኋት በለንደን የእሳት ልጅ እሳት ሆና
የደም አዙሪት ምሬቱ
የእሳት ትግል ሽረቱ
እየፈላባት ሐሞቷ እየታገላት ሲቃ
ታቦቷን ከራሷ ሳይሆን ከደረቷ ላይ ደብቃ
ተሻገረችው ያንን ጉድ አስለቀሰችን ነፍርቃ
ጀመረች አግዥኝ ብላ
ድንግልን በደረቷ አዝላ
ታሪክ ናት ይህች ማርያም ለተማጸናት በብርቱ
ልጇን ላመነ በልቡ ፍቅሯን ላሰረ በአንገቱ
ረሳችውና ድካሟን የልፋት ውጤት ወርቋን
ከፍ አደረገች በሥዕሏ የድንግል ማርያምን ስሟን
ግሸን ሆነች አሉ ለንደን ተቀይራ
መሠረተ ሕይወት ድንግል ተዘምራ
እምነት ከጉያ ውስጥ ድንገት ፈለቀና
ሃሌ ሃሌ ሆነ ድካም ተረሳና
የእኛ ርግብ አማኝቷ
የኢትዮጵያ ልጅ መሠረቷ
ቢላላባት ያሰረችው ቢበጣጠስ መቀነቷ
ተወራርዳ አሸነፈች በጌታ እናት በአዛኚቷ
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ለመጋቢት16 ዝክር የተጻፈ
2008 ዓ.ም
አዲስ አበባ